Sunday, August 24, 2014

‹‹በያዛችሁትን ስልጣን ቤተክርስትያንን ከውድቀት ልታነሱበት ይገባችኋል ፤ ይህ ሳይሆን ከድጡ ወደ ማጡ የምትወስዷት ከሆነ ከታሪክ ተወቃሽነት አትተርፉም›› አለቃ አያሌው ታምሩ


አንድ አድርገን ነሐሴ 17 ፤ 2004 ዓ.ም 
፡- 
ቀኑ ህዳር 6 1985 ዓ.ም ነበር ፡፡ በአዲስ አበባ ከተማ ሰሜን አቅጣጫ በምትገኝው በመንበረ መንግስት ቁስቋም ቤተክርስትያን ብዙ ህዝበ ክርስትያን ተሰብስቧል ፡፡ ምክንያቱ በዓለ ቁስቋምንና የጾመ ጽጌን ፍቺ በዓል ለማክበር ነበረ ፡፡ የዕለቱም አስተማሪ አለቃ አያሌው ታምሩ ነበሩ፡፡ አለቃ ‹‹በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን›› ብለው ጀመሩ፡፡ በትምህርታቸውም ስለ እመቤታችን ስደት ፤ ስለ ቁስቋም ታሪክ ፤ ወደ እየሩሳሌም ስለ መመለሷ ፤ ከእመቤታችን 300 ዓመት በኋላ በግብጽ ስለተሰራው የመታሰቢያ ቤተክርስትያን ፤ በዚህ በዓል ምክንያት ኢትዮጵያውያን ነገስታትና ንግስታት ስላደረጓቸው መንፈሳዊ ተሳትፎዎች ፤ ስመ ጥሩዋ ኢትዮጵያዊት ንግስት እቴጌ ምትዋብ በጎንደር ስላሰሯት የደብረ ቁስቋም ቤተክርስትያን  ፤ ስለ ጾመ ጽጌ ፤ ስለ ማህሌተ ጽጌ በዝርዝር አስተማሩ፡፡ ከዚያም በመቀጠል ፤ በእመቤታችን በቅድስት ማርያምና በልጇ ስደት በረከትን ካገኙ የኢትዮጵያ አውራጃዎች አንዱ የሆነው ምድረ ትግራይ ከሌሎች ቅዱሳን የኢትዮጵያ መካናት ጋር የተጣመረ የታሪክ ተዛምዶ ያለው ከመሆኑ ባሻገር ከታቦተ ጽዮን ጀምሮ ለኢትዮጵያ ለተሰጡ ልዩ ልዩ ስጋዊ እና መንፈሳዊ በረከቶች ምንጭና ቦይ ሆኖ የኖረ ነው ፡፡ ዋልድባ ገዳምም ይህን መንፈሳዊ በረከት ከሚገኝባቸው ቦታዎች አንዱ ነው ፤  በአሁኑ ወቅት ህዝቡ የተሰጠውን  ስጋዊ ስልጣን አገሪቱንና ቤተክርስትያንን ከውድቀት ለማንሳት ሊሰራበት ይገባል፡፡ ይህ ሳይሆን ቀርቶ ህዝብና እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ስራ ቢሰራ ግን ትዝብትና የታሪክ ተወቃሽነትን ያተርፋል ፤ ያለው ሰፊት ትምህርት ሰጥተዋል ፡፡(የአለቃ አያሌው ታምሩ የመንፈቅ መታሰቢያ ገጽ 26)
የአባታችን አለቃ አያሌው ታምሩ ይህን ለምን እንዳሉ ግልጽ ነው ፤ ዘመነ ደርግ የሰራዊት ብዛት መከታ ሳይሆነው ከትግራይ የተነሱት የሽምቅ ተዋጊዎች ዘንድ ስልጣል በእጃቸው ገብቷል ፤ ዘመነ ደርግ ቤተ ክርስትያን ከዩዲት ጉዲት እና ከግራኝ መሀመድ በኋላ በአገዛዙ ከፍተኛ ፈተና ላይ የወደቀችበት ጊዜ ነበር ፤  እግዚአብሔር የለም የተባለበት ጊዜም ነበር ፤ ኢትዮጵያ ሀገረ እግዚአብሔር እና እመቤታችን የአስራት ሀገር ብሎ በአውደ ምህረት መስበክ ለአገልጋዮች አስቸጋሪ ወቅት ነበር ፡፡ የእምነት ነጻነት ሀውልት ባይሰራለትም  ለ17 ዓመት የተቀበረበት ጊዜ ነበር ፤ ሀገሪቱም በጊዜው የተረጋጋች አይደለችም ፤  አለቃ አያሌው ማስተላለፍ የፈለጉት መልዕክት ‹‹የያዛችሁትን  ስልጣን ቤተክርስትያንን ከውድቀት ልታነሱበት ይገባችኋል ፤ ይህ ሳይሆን ቢቀርና ቤተ ክርስትያንን ከድጡ ወደ ማጡ የምትወስዷት ከሆነ ፤ ለችግሯ የመፍትሄ አካል ባትሆኑ እንኳን የሚነደው እሳት ላይ ማገዶ የምትማግዱባት ከሆነ ፤ እግዚአብሔርንም የሚያሳዝን ስራ ከሰራችሁ ከታሪክ ተወቃሽነት አትተርፉም››  ነው ያሉት፤

በታሪክ አጋጣሚ ሰዎች ስጋዊ ስልጣን ሊኖራቸው ይችላል ፤  ስልጣናችሁን ለሀገር ፤ ለህዝብና ለቤተክርስትያን መልካም በመስራት ካሳለፋችሁ ጊዜያችሁን እንደ ንጉስ ሰለሞን ዘመናችሁ በረከት ይኖረዋል ፤ ንጉስ ሰለሞን ከአባቱ ዳዊት ንግስና ሲቀበል መጀመሪያ እግዚአብሔርን እንዲህ ብሎ ለመነ

‹‹ አቤቱ አምላኬ ሆይ፥ እኔን ባሪያህን በአባቴ በዳዊት ፋንታ አንግሠኸኛል እኔም መውጫንና መግቢያን የማላውቅ ታናሽ ብላቴና ነኝ። ባሪያህም ያለው አንተ በመረጥኸው ሕዝብህ ስለ ብዛቱም ይቆጠርና ይመጠን ዘንድ በማይቻል በታላቅ ሕዝብ መካከል ነው። ስለዚህም በሕዝብህ ላይ መፍረድ ይችል ዘንድ፥ መልካሙንና ክፉውንም ይለይ ዘንድ ፤ ለባሪያህ አስተዋይ ልቡና ስጠው አለዚያማ በዚህ በታላቅ ሕዝብህ ላይ ይፈድ ዘንድ ማን ይችላል?›› መጽሐፈ ነገሥት ቀዳማዊ 3 ፤9

‹‹እግዚአብሔርም አለው፦ ፍርድን ትለይ ዘንድ ለራስህ ማስተዋልን ለመንህ እንጂ ለራስህ ብዙ ዘመናትን ባለጠግነትንም የጠላቶችህንም ነፍስ ሳትለምን ይህን ነገር ለምነሃልና እነሆ፥እኔ እንደ ቃል አድርጌልሃለሁ እነሆ፥ ማንም የሚመስልህ ከአንተ በፊት እንደሌለ ከአንተም በኋላ እንዳይነሣ አድርጌ ጥበበኛና አስተዋይ ልቡና ሰጥቼሃለሁ።››  መጽሐፈ ነገሥት ቀዳማዊ 3 ፤11-12 አለው ፤

‹‹በአሁኑ ወቅት ህዝቡ የተሰጠውን  ስጋዊ ስልጣን አገሪቱንና ቤተክርስትያንን ከውድቀት ለማንሳት ሊሰራበት ይገባል፡፡ ይህ ሳይሆን ቀርቶ ህዝብና እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ስራ ቢሰራ ግን ትዝብትና የታሪክ ተወቃሽነትን ያተርፋል›› አለቃ አያሌው ታምሩ



እግዚአብሔር ለመሪዎች ማስተዋል እና ጥበቡን ይስጣቸው



2 comments:

  1. iwnet new እግዚአብሔር ለመሪዎች ማስተዋል እና ጥበቡን ይስጣቸው
    leinantem tena ina rejim idmie yadililin
    Amen

    ReplyDelete
  2. Very important message to those who are given the opportunity of power to save Ethiopia and the Tewahdo Church. They can use the power to do good or to do evil. Time will pass and what they did
    will reflect on them. May the Lord give them understanding/.

    ReplyDelete