Thursday, July 14, 2016

በስማቸው አብያተ ክርስቲያኒያቱን ያስመዘገቡ እጩ ጳጳሳት


ከጀርመን ምዕመናን የደረሰን
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በመጪው ጥቅምት በሚያካሂደው ርክበ -ካህናት ለመሾም ያሰባቸውን አባቶች ምዕመኑ ሃሳቡን እንዲሰጥበት መወሰኑ የሚያስመሰግነውና ከሃሜት ለመራቅ የሚያስችለው በመሆኑ ተገቢነቱን እንገነዘባለን። የተሰጠንን እድል በመጠቀምም የምዕመንነት ድርሻችንን መወጣት አለብን ብቻ ሳይሆን ይገባናልም።
 
ማንም ኤጲስ ቆጶስነትን ቢፈልግ መልካምን ስራ ይመኛል የሚለው ቃል የታመነ ነው።እንግዲህ ኤጲስ ቆጶስ እንዲህ ሊሆን ይገባዋል።የማይነቀፍ ልከኛ ራሱን የሚገዛ እንደሚገባው የሚመራ እንግዳ ተቀባይ ለማስተማር የሚበቃ ገር የሆነ የማይጨቃጨቅ የማይከራከር ገንዘብ የማይወድ ልጆቹን በጭምትነት ሁሉ እየገዛ የራሱን ቤት በመልካም የሚያስተዳድር ፤ ሰው ግን የራሱን ቤት እንዲያስተዳድር ባያውቅ የእግዚአብሔርን ቤት እንዴት ይጠብቃል? 1ኛ ጢሞ.3፡1-5 ይላል።

 
ይህንን የአምላካችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቃል መሰረት በማድረግ ከጀርመን አገር ከተጠቆሙት አባቶች መካከል አባ ገብረሕይወት ከሙኒክ፤አባ ብርሃነ መስቀል ከበርሊን ብቃት ያላቸውና ይደልዎ የተባለላቸው አባቶች ስለሆኑ እስካሁን ጳጳስ ሳይሆኑ መቆየታቸው እንጂ በጥቆማው ላይ ብቃታቸውም መንፈሳዊ ሕይወታቸውም የትምህርት ዝግጅታቸውም ቢመረጡ ቤተክርስቲያንንና አገራችንን ሊጠቅሙ የሚችሉ ናቸው።በዚህም በነዚህ አባቶች መባረክ መታደል ነው።
 
ነገር ግን በቀሪዎቹ ሁለት አባቶች ላይ ከፍተኛ ቅሬታ አለብን። በመጀመሪያ አባ ሲራክ የፍራንክፈርት ቅድስተ ማሪያም ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪን በተመለከተ፡- በመጀመሪያ ሲራክ ብሎ የቆሞስ ስም የለም።አገር ቤት በነበሩበት ወቅት አባ ሃይለመለኮት ተስፋማርያም ነበር የሚባሉት ጀርመን አገር ከመጡ በሁዋላ ለኬዛቸው ብለው ስማቸውን ቀይረው ሲራክ ተብለዋል።እሺ ለወረቀት ብለው ያደረጉት ስለሆነ እንደፈቃዳቸው ብለን እንለፈው።ሆኖም እዚህ አገር ያለው ምዕመን የሚያውቃቸው አባ ሲራክ በሚለው በመሆኑ ተገቢ ባይሆንም ያለውን ጎናዊ ጫና በማየት አገረ ስብከቱ እድላቸውን ይሞክሩ ብሎ በዚሁ ስማቸው ነበር የላካቸው ግን እሳቸው አገር ቤት ድረስ ከወር በላይ በመቆየት በድሮ ስማቸው አስቀይረውት ይፋ ሆኖ እያየነው ነው።አንደኛ የጀርመን ምዕመን አባ ሃይለመለኮት የሚባሉ አባት ስለማያውቅ የሌሉ ሰው ናቸው በመወዳደር ላይ ያሉት ይቀነሱልን።አይ በሁለተኛ ስማቸው የምናውቃቸው እሳቸው ከሆኑ ደግሞ በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ ነውና ነገሩ ስለ ቤተክርስቲያን ስንል ለአስመራጭ ኮሚቴውና ለመላው ሕዝብ ገመናቸውን እንገልጣለን።
 
የቤተክርስቲያናችን ቀደም አባቶች የሆኑት ጳጳስነት ሊሾሙ እንደሚፈለጉ ሲያውቁ ይሸሻሉ ይደበቃሉ አካላቸውን ያጎድላሉ እነ አባ ሲራክ ግን አገር ቤት ድረስ ሄደው ለመሾም ምልጃ በወቅቱ ቋንቋ በድሮ ስማቸው ሎቢ ያደርጋሉ።ይሄ በራሱ ምልጃ የተሄደባቸው አባቶች በምስጢር በሚሰጠው ድምፅ ድምፃቸውን እንደሚነፍጓቸው እንጠብቃለን በፊት ለፊት መጋፈጥ ቢያቅታቸው ማለታችን ነው።በእኛ እምነት እንኳንስ ሊወዳደሩ ሊጠቆሙ እንኳን አይገባቸውም -አባ ሲራክ።


ምክንያቱም፡- አባ ሲራክ
  • በጎጥ ምዕመኑን በመከፋፈልና የሙስና ችግሮቻቸው እንዳይጋለጥ ሲሉ የቤተክርስቲያን ልጆችን ከፍራንክፈርት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አባረዋል።
  • አዲስ ቤተ ክርስቲያን እንዲፈጠር በማድረግ የቤተ ክርስቲያኒቱን አንድነት አናግተዋል።
  • በማስተዳደር ላይ በሚገኙት ቤተ ክርስቲያን ከምዕመናን የሚሰበሰበውን ገንዘብ ለግል ጥቅማቸው አውለዋል ፤ በማዋል ላይም ናቸው።
  • የሰበካ ጉባኤውን በፈለጉት ጊዜና በሚፈልጓቸው ሰዎች በመተካት ሰንበት ትምህርት ቤቱንም አፍርሰዋል በአጭሩ ቤቱን በአምባገነንነት  እየመሩት ይገኛሉ።
  • የቤተክርስቲያኗ ሂሳብ ተወራርዶ የማያውቅ ከመሆኑም በላይ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተራቆተ በመምጣቱ በአሁኑ ወቅት ለራሳቸው ደሞዝ እንኳን መክፈል አቅቷቸው ምዕመኑ በየጊዜው እያዋጣ እየደጎመ ይገኛል።
  • በቤተክርስቲያኗ ገንዘብ የተገዛችውን መኪና በስማቸው አድርገው ወጪዋን ሁሉ ከደሞዛቸው ውጭ በተጨማሪ ከቤተ ክርስቲያኗ ወጪ እያደረጉ አሁንም እየተገለገሉ ናቸው።
  • በቅርቡ የቤተ ክርስቲያኗ አቅም ሲዳከም ብር ማጣት ሲጀመር ለመጀመሪያ ጊዜ ከ16 ዓመት በሁዋላ የባንክ ቡኩን ቤተ ክርስቲያኗን ለማዳን ለተቋቋመው ኮሚቴ አስረክበዋል።
አያድርገው እንጂ የሆነ ችግር ቢፈጠር ቤተ ክርስቲያኗንም በስማቸው ያስመዘገቧት በመሆኑ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ንብረት ናት ብሎ የሚያስረክብ የለም።በአገሪቱ ሕግ በማህበር የተመዘገበችና ንብረትነቷም የኢ/ኦ/ተ/ቤ መሆኑ የተረጋገጠ ማስረጃ የለም።ለዚህም ነው ክስ ሲነሳባቸው በስማቸው የተመዘገበ ንብረት ነው በሚል ሰሚ የማያገኘው።ወደፊት የሚመለከተው አካል ይህንን ማስተካከልና ቤተ ክርስቲያኗን ማዳን ይገባል እንላለን።

ሌላው አባ ሲራክ ቤተክርስቲያኗንና ፍራንክፈርት የሚገኘውን ቆንስላ ጀነራል ጽሕፈት ቤት ስራ ቀላቅለው የሚመሩ ይመስል አንተ ተቃዋሚ አንተ ፈሪ አንተ ደጋፊ በሚል ከመንፈሳዊ ሕይወታቸው ወጥተው ጭምር የማይመለከታቸውን ተግባራት በማከናወን ካላት እድሜ አኳያ ትልቅ ደረጃ መድረስ የሚገባትን ቤተክርስቲያን እንድታሽቆለቁል አድርገዋታል።  

አላስፈላጊ ጥቅማጥቅሞችን በማካበትም ደህና ሃብት ያፈሩ መሆናቸው ይነገራል።በአገር ቤት ያላቸው ንብረት ከአንድ መነኩሴ የማይጠበቅ ነው።በጣም የሚያሳዝነንና የሚያሳፍረን ግን የቤተክርስቲያኗን መርህ በመተላለፍ በቪዝባደን ቅዱስ ጊዮርጊስ አስተዳዳሪ ከነበረው የፕሮቴስታንት ልኡክ ጋር በመሻረክ ቅድስት ማርያም ቆሞ የኑፋቄ ትምህርቱን እንዲያስተምር በተደጋጋሚ ከምዕመኑና ከቀድሞው ሊቀጳጳስ የተሰጣቸውን መመሪያ በመጣስ ቤተ ክርስቲያንን ሲያስደፍሩና ሲያረክሱ የነበሩ ሰው ናቸው።ጓደኝነትና ጥቅምን ከቤተክርስቲያን አብልጠው  በቤተክርስቲያን ላይ ያመፁና ሲያሳምፁ የነበሩ ናቸው። በነገራችን ላይ በሙስና ጉዳይ ፍርድ ቤት ክስ ተመስርቶባቸው ነበር። የቅርብ ጊዜውን እንኳን ሙስና ማየት ቢፈለግ የአገረ ስብከቱን ሊቀጳጳስ ላስተናግድበት ነው በሚል 2 ሺ ይሮ አውጥተው ለግል ጥቅማቸው አውለዋል።
በተጨማሪም ቤተክርስቲያኗ በዘፈቀደ የምትመራና የተዝረከረከ አሰራርን የሚከተሉ መሆናቸው እንኳንስ ጳጳስ ሆነው አገረ ስብከት ሊመሩና አንድ አጥቢያ ቤተክርስቲያንን የሚያስተዳድር አቅም የትምህርት ዝግጅትና ዘዴውም የማያውቁት በመሆናቸው በጥቂቱ ገንዘብ የማይታመኑት አባ ወደ ትልቁ ገንዘብማ ሲሄዱ ጉድ ሊያፈሉ እንደሚችሉ በመገንዘብ አስመራጭ ኮሚቴው ከፈለገ የጀርመንን ህዝብ ሰብስቦ ሊጠይቅና ሊያረጋግጥ የሚችለው በመሆኑ ከጥቆማው ዝርዝር ውስጥ እንዲያስወጣቸው እንጠይቃለን። 

ሁለተኛው አባ ስብሓት ለአብን በተመለከተ እኚህ አባት በኢ/ኦ/ተ/ቤ ስር የማይተዳደሩ በዚሁ ጀርመን አገር ገለልተኛ የተባለ የቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን አቋቁመው በተደጋጋሚ ወደ እናት ቤተክርስቲያናቸው እንዲመለሱ በወረዳው ቤተክህነት በአገረ ስብከቱና በቅዱስ ሲኖዶስ ደብዳቤ ጭምር ሲጠየቁ አሻፈረኝ ብለው በማን አለብኝነት የቤተክርስቲያናችንን ስም ይዘው ከቤተክርስቲያን ያፈነገጡ አባት ናቸው። እንዴት ተጠቆሙ? ማን ጠቆማቸው? እግዚአብሔር ይወቅ ሲሆን ራሳቸውን በደብዳቤ ከጥቆማው ማግለል ነበረባቸው ካልሆነ ግን እውነቱ ይህ መሆኑ ታውቆ በጭራሽ ለውድድር እንዳይቀርቡ ይደረግልን።የአገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስም ይህንኑ ስለሚያውቁ መጠየቅ ይቻላል።

አገረ ስብከቱ የማያውቃቸውን ብሎም ከመስመር ውጭ ያሉ አባት ለውድድር ማቅረብም የሚያስተዛዝብ በመሆኑ እኛን መንጋዎቻቸውን የሚጠብቁ እረኞች ተኩላዎች እንዳይሆኑብን አስመራጭ ኮሚቴው የቀረቡትን አባቶች ማንነት በደንብ ሳያጣራ ከሚያስበላን እንዲጠነቀቅ እንጠቁማለን።እናንተ ከፍተኛ የክርስቶስ አደራ ያለባችሁ አባቶች ስለ ቅድስት ቤተክርስቲያናችሁ ብላችሁ መልካም እረኞችን አንጠርጥራችሁ ለዩልን።

ስብሓት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር አሜን ይቆየን !!!  

      ከ60 በላይ ምዕመናን ከላይ በተጠቀሱን አባቶች ላይ የጵጵስና ማዕረግ አይገባቸውም በማለት ፊርማ አሰባስበው ልከውልናል..እነሆ






4 comments:

  1. አሰመሳዩና ከሀዲው መነኩሴ ነኝ ባዩ ሢራክ ለጵጵስና መቅረቡ በራሱ አስገራሚ ነዉ ፀረ ቅዱሳን፣ ሞያ ቢስ፣ ሐኬተኛና አድመኛ እውነት ለመናገር፣ አባ ሢራክ ስንፍና ብቻ ሳይሆን ሞያም የላቸውም። ድፍረት ባይሆንብን፣ አባቶች ከፊታችሁ አስቀርባችሁ፣ እንደ ሊጦን፣ መስተብቁዕ…ከአባቶች ፊት ቀርበው ኣንድ ውዳሴ ማርያም ቢጠየቁ የማይወጡ ናቸው የቅስና ሞያ ብትጠይቋቸው ያን ጊዜ ትረዷቸዋላችሁ። ይህን ሁኔታ ማለትም ስንፍናቸውንና በቂ ዕውቀት የሌላቸው ናቸው

    ReplyDelete
  2. ሰላም አንድ አድርገኖች ይሄንን ጽሁፍ ያገኘሁት የተዋሕዶ ቤተሰቦች ከሚባል የጡመራ መድረክ ላይ ነው እኚህም አንደኛው ለጵጵስና ተጠቋሚ መነኮሴ ናቸውአባ ገብረ ኪዳን ይባላሉ በላስ ቬጋስ ሐመረ ኖህ ኪዳነ ምሕረት ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪ ናቸው ዝርዝሩን ከዚህ ብሎግ ታገኙታላችሁ ለማንኛውም በምንም በኩል የቀበሮ ባሕታውያን አለፈው ከትልቁ የቤተክርስቲያናችን ማዕረገ ጵጵስና ላይ እንዳይደርሱ ማድረግ የሁላችንም ሃላፊነት እንደሆነ በማመን ነው። ብዙ ብቃትም ቅድስናም ያላቸው ቅዱሳን አባቶች ሞልተው እያለ ነገር ግን ዝም ተብሎ በሙስና ስማቸውን እዚህ ውስጥ ማስገባት ሰዎችን ሕሊና ቢስ ያስብላቸዋል እና ጥንቃቄ እንድናደርግ አደራ ለማለት እንወዳለን
    http://yetbet.blogspot.com/2014/02/blog-post.html

    ReplyDelete
  3. የድሮው ሀይለመለኮት የአሁኑ አባ ሲራክ የኣገራቸው ልጅ ጳጳስ አባ ሙሴ በመሆናቸው ምክንያት ከሀያ አመት በላይ የቤተክርስቲያን ገንዘብ ሲዘርፋ በስነምግባር የወደቁ ዝሙተኛ በሐይማኖት ስም ፓለቲካ የሚያራምዱ ዘረኛ ቀንደኛ የአማራ ጠላት ናቸው እኒህ ነው በምግባር የወደቁ ዘማዊ በፍቅረ ንዋይ የተጠመዱ ሌባ ለሀይማኖት ግድ የሌላቸው ሙያቢስ መሀይም ለታላቁ የቤተክርስቲያን ማእርግ መጠቆማቸው አሳፋሪ ከመሁኑም በላይ የአባ ሙሴ ነገር መጠናት ያለበት ነው

    ReplyDelete
  4. አንድ አድርገኞች ይህ ቤተክርስቲያንን ለመጥቀም ሳይሆን አባ ሲራክን ለመበቀል የተጻፈ ኢክርስቲያናዊ ጽሑፍ በመውጣቱ እና እዚህ ላይ ብፁዕ አቡነ ሙሴን የሚዘልፍ ስድብ ሲጻፍ (comment ሲደረግ) ዝም ማለታችሁን ከእናንተ ያልጠበኩት ሆኖብኛል::

    በመጀመሪያ ይህ ጽሑፍ የወጣው አባ ሲራክ በአንደኛው ዙር ማጣሪያ ከቀሩ በሁአላ በመሆኑ ጽሁፉን መለጠፍ ለምን አስፈለገ?
    ሁለተኛ የምአመናንን ፊርማ በማውጣት ማን ማን እንደፈረመ ለዓለም በማሳየት ፈራሚዎቹን ከአባ ሲራክ እና ከደጋፊዎቻቸው እንዲሁም የተጻፈው ጽሑፍ አግባብ አይደለም ብሎ ከሚያምን ከእንደኔ አይነት ምእመን ጋር ቅራኔ ውስጥ ማስገባት ለምን አስፈለገ?
    ሦስተኛ ከፊርማው በላይ ያለውን ፈራሚዎቹ የፈረሙበትን ጉዳይ የሚገልጸው ዐረፍተ ነገር ለምን አብሮ ስካን ሳይደረግ ቀረ? (ይህንን ያልኩት አብዛኞቹ ምእመናን የፈረሙት አባ ሲራክ እና አባ ስብሐት ለአብ ለጵጵስና ማእረግ መታጨታቸውን በመቃወም እንጅ አስተባባሪዎቹ በሁአላ አርቅቀው ለእናንተ የላኩትን እና እናንተ እንደወረደ የለጠፋቹትን ጥላቻ የተሞላበት ዘለፋ በመደገፍ እንዳልሆነ ሰለሚታወቅ ነው)
    አራተኛ ከአባ ሲራክ አልፎ ብፁዕ አቡነ ሙሴን የሚዘልፍ comment እንዲለጠፍ ለምን ፈቀዳችሁ??? ስህተታችሁን እንደምታርሙ ተስፋ አደርጋለሁ:: ካለዚያ በማላውቃቸው አባቶች ላይ የምታወጡት መረጃ እንደዚህ የተዛባ ላለመሆኑ ምን ማስተማመኛ አለኝ???

    ReplyDelete